25/05/2022
+ ቅዱስ ዶክተር ሉቃስ +
መጽሐፍ ቅዱስን እጅግ አስደናቂ መጽሐፍ ከሚያደርጉት ብዙ እውነታዎች አንዱ ሃሳቡ አንድ ሆኖ ሳለ የጸሐፊዎቹ ማንነት ግን እጅግ የተለያየ መሆኑ ነው፡፡ እረኞች ፣ ነገሥታት ፣ ዓሣ አጥማጆች ፣ ሰዓሊዎች ፣ የሂሳብ ባለሙያዎች ፣ ገበሬዎች ፣ ድንኳን ሰፊዎች ፣ ሐኪሞች በአጠቃላይ የተለያየ ሙያ ያላቸው ሰዎች ነበሩ - ጸሐፊዎቹ፡፡ ከእነዚህ ብዙ ጸሐፍት ውስጥ የሦስት ሙያዎች ባለቤት የሆነው ጠቢቡ ቅዱስ ሉቃስ ይገኝበታል፡፡ ይህ ወንጌላዊ በሙያው ጸሐፊ ፣ ሰዓሊ እና ሐኪም ነበረ፡፡
‹ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ› በተጨማሪም በወንጌሉ ላይ ሐኪምነቱን የሚያስረዱ ብዙ አሻራዎችን አስቀምጧል፡፡ (ቆላ. 4፡14) የጸሐፊያንን ማንነት በጽሑፋቸው ውስጥ ፈልጎ ማግኘት የመጽሐፍ ቅዱስ ሊቃውንት አንዱ ጥበብ ነው፡፡ ለምሳሌ የዕብራውያን መልእክትን ቅዱስ ጳውሎስ እንደጻፈው በመልእክቱ ላይ አልተናገረም ነበር፡፡ ይህንንም ያደረገው ዕብራውያን ለእርሱ ባላቸው ጥላቻ ምክንያት መጽሐፉን ሳያነቡት እንዳይቀሩ ብሎ ነበር፡፡ ታዲያ ‹እሱ መጻፉን ካልተናገረ እኛ በምን አወቅነው?› ብትሉ የዕብራውያንን መልእክት ሲጨርስ በጻፋት ‹‹ጸጋ ከሁላችሁ ጋር ይሁን›› በምትለዋ የመዝጊያ ሰላምታው ነው፡፡ (ዕብ. 13፡ 25) በዚህ ሰላምታ ብቻ እንዴት ማረጋገጥ ይቻላል ቢባል ደግሞ ራሱ ቅዱስ ጳውሎስ ይህቺን የምሥጢር ሰላምታ አስመልክቶ ‹‹በገዛ እጄ የተጻፈ የእኔ የጳውሎስ ሰላምታ ይህ ነው፤ የመልእክቴ ሁሉ ማስረጃ ይህ ነው፤ እንዲህ እጽፋለሁ። የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከሁላችሁ ጋር ይሁን።›› በማለት ተነግሮ ስለነበረ ነው፡፡ (2ተሰ. 3፡18)
ቅዱስ ሉቃስም በወንጌሉ ላይ ወንጌሉን ራሱ እንደጻፈው የሚያረጋግጡ ምልክቶችን ትቶልናል፡፡ ከእነዚህ ምልክቶች ውስጥ አንዳንዶቹ እንደ ሉቃስ በሙያቸው ሐኪም ለሆኑና በግሪክ ቋንቋ የሚነገሩ የሕክምና ሙያዊ ቃላትን የሚያውቁ ሰዎች ብቻ ሊረዷቸው የሚችሉ ሲሆኑ ሆባርት የተባለ እንግሊዛዊ ጸሐፊ ''The medical language of St. Luke'' (የቅዱስ ሉቃስ ህክምናዊ ልሳን) በሚል ርዕስ በጻፈው መጽሐፍ ላይ በሉቃስ ወንጌል ውስጥ ያሉ የሕክምና ሙያዊ ቃላትን እንደ ሂፖክራተስ ካሉ የግሪካዊያን ጸሐፍት ሥራዎች ጋር ያመሳክራል፡፡ ከቅዱስ ሉቃስ ሐኪማዊ አገላለጾች አንዳንዶቹ ደግሞ ስለ ሕክምና ብዙም እውቀት ሳይኖረንም ልንረዳቸው የምንችላቸው ናቸው፡፡
በርኩስ መንፈስ ይሰቃይ የነበረ አንድ ሰውን ታሪክ በማርቆስ ወንጌል የመጀመሪያ ምእራፍ ላይ እናነባለን፡፡ በዚያን ጊዜም በምኩራባቸው ርኵስ መንፈስ ያለው ሰው ነበረ፤ እርሱም፦ የናዝሬቱ ኢየሱስ ሆይ፥ ከአንተ ጋር ምን አለን? ልታጠፋን መጣህን? ማን እንደ ሆንህ አውቄአለሁ፥ የእግዚአብሔር ቅዱሱ ብሎ ጮኸ። ኢየሱስም፦ ዝም በል ከእርሱም ውጣ ብሎ ገሠጸው። ርኵሱም መንፈስ አንፈራገጠውና በታላቅ ድምፅ ጮኾ ከእርሱ ወጣ።›› ይላል፡፡ (ማር.1፡25-26) ይህንኑ ታሪክ ወንጌላዊው ሉቃስ ሲጽፈው ግን እንዲህ ነበር ያለው ‹‹ኢየሱስም፦ ዝም በል ከእርሱም ውጣ ብሎ ገሠጸው። ጋኔኑም በመካከላቸው ጥሎት ሳይጐዳው ከእርሱ ወጣ።›› (ሉቃ. 4፡35) ቅዱስ ማርቆስ ጌታ ጋኔኑን ሲያወጣ ምን እንደተከሰተ ሲጽፍ ‹‹ርኩስ መንፈሱም በታላቅ ድምጽ ጮኾ ከእርሱ ወጣ›› በማለት የጋኔኑ አወጣጥ ላይ አተኩሮ ሲጽፍ ሐኪሙ ሉቃስ ግን ‹‹ጥሎት ሳይጎዳው ወጣ›› ብሎ የጋኔኑ አወጣጥና የበሽተኛው አወዳደቅ ጉዳት የሚያደርስ ስለመሆኑና ስላለመሆኑ ተጨንቆ ጻፈ፡፡ ስለ ታካሚ ደህንነት (patient safty) ማሰብ ይሏል ይኼንን ነው፡፡
የቅዱስ ጴጥሮስ አማትስ በምን እንደታመመች እናስታውስ ይሆነን? ቅዱስ ማርቆስና ቅዱስ ማቴዎስ ሕመሟን ሲገልጹ ሁለቱም ‹‹በንዳድ ታማ ነበር›› ብለዋል፡፡ (ማቴ. 8፡14 ፤ ማር. 1፡30) ሐኪሙ ሉቃስ ግን ‹‹በብርቱ ንዳድ ታማ ነበር›› በማለት በባለሙያ አገላለጽ አስቀምጦታል፡፡
ሌላው ተጠቃሽ ነገር ለሙያ አጋሮቹ ክብር ሰጥቶ ወግኖ የተናገረበት ሥፍራ ነው፡፡ አሥራ ሁለት ዓመት ደም ይፈስሳት ስለነበረችዋ ሴት ያልተሳካ ሕክምና ቅዱስ ማርቆስ ሲገልጽ ‹‹ከብዙ ባለ መድኃኒቶችም ብዙ ተሠቃየች፤ ገንዘብዋንም ሁሉ ከስራ ባሰባት እንጂ ምንም አልተጠቀመችም›› በማለት የሐኪሞቹን ድርሻ በማያሳይ አሉታዊ አገላለጽ ነበር፡፡ (ማር. 5፡25) የሐኪምን ነገር የሚውቀው ሉቃስ ግን ‹‹ትዳርዋንም ሁሉ ለባለመድኃኒቶች ከስራ ማንም ሊፈውሳት አልተቻለውም።›› በማለት ኪሳራዋ እንዳለ ሆኖ ሐኪሞቹ ግን ያላዳኗት ስላልቻሉና ከአቅማቸው በላይ ስለሆነ መሆኑንም ጨምሮ ጽፏል፡፡ (ሉቃ. 8፡43) ቅዱስ ሉቃስ በወንጌሉ ላይ ከዚህ በተጨማሪ የሕክምናን ሒደት የሚያሳዩ ቁስል ማጠብን ፣ ዘይት ማፍሰስን ፣ በጨርቅ ማሰርን ፣ በትኩሳት ላይ ያለ ሰው ከንፈሩ እንዲርስለት የሚፈልግ ስለመሆኑ ፣ በቁስል ስለመወረስ ወዘተርፈ የሚተርኩ ምሳሌዎችን እና ታሪኮችን በጥንቃቄና ሙያዊ ቃላትን በሚያሳይ አጻጻፍ ሲያስቀምጣቸው እናገኛለን፡፡
መድኃኔዓለም ክርስቶስ በጌቴሴማኒ ሆኖ ሲጸልይ የነበረውን ጭንቀት ቅዱስ ሉቃስ ሲጽፍ ‹‹በፍርሃትም ሲጣጣር አጽንቶ ይጸልይ ነበር፤ ወዙም በምድር ላይ እንደሚወርድ እንደ ደም ነጠብጣብ ነበረ።›› ብሎ ጽፎአል፡፡ (ሉቃ. 22፡44) የጌታችንን ወዝ እንደ ደም ነጠብጣብ ስለመሆኑ ብዙ ሊቃውንት የወዙን አፈሳስና መወየብ ለመግለጽ የተቀመጠ ንጽጽር ነው እንጂ ድ አይደለም በማለት ያብራሩታል፡፡
የሕክምና ሰዎች ግን ይህን ወዝ ራሱ የደም ነጠብጣብ ነው የሚለው ሃሳብ ላይ በማዘንበል በሳይንሳዊ መንገድ ያብራራሉ፡፡ የሰው ልጅ ውስጣዊ መታወክ እና ከፍተኛ ጭንቀት ሲደርስበት ከሰውነቱ በላብ ፈንታ ደም ይወርደዋል፡፡ ይህ የደም ላብ የመከሰት እድሉ በጣም አነስተኛ ቢሆንም ለዚህ የደም ላብ የሕክምና ሰዎች የሚጠቅሱት ማሳያ ምሳሌ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ስለሁላችን በተጨነቀበት ሰዓት የወረደውን ወዝ ነው፡፡ ሐኪሞቹ ይህን ክስተት ሄማቶድሮሲስ (Hematodrosis) በማለት ይጠሩታል፡፡ ሊቁ ቅዱስ አውግስጢኖስም የሐኪሞቹን ሃሳብ የሚደግፍ ንግግርን ተናግሯል፡፡ በሊቁ ትርጓሜ ‹‹ከጌታ ሰውነት እንደ ወዝ የፈሰሰው ደም የክርስቶስ አካል ከሆነች ከቤተ ክርስቲያን የሚፈስሰው የሰማዕታት ደም ምሳሌ ነው፡፡››
ሐኪሙ ቅዱስ ሉቃስ በቀጥታ ባይጽፋቸውም በወንጌሉ ውስጥ ከሕክምና አንጻር ሊተነተኑ የሚችሉ ሌሎች መንፈሳዊ እውነታዎችንም ጽፎአል፡፡ አንዱን እንመልከትና እናብቃ፡፡ በሉቃስ ወንጌል ከተመዘገቡ የመጀመሪያ ታሪኮች አንዱ የመጥምቁ ዮሐንስ እንደ ኦሪት ሕግ በተወለደ በስምንተኛው ቀን መገረዝ ነው፡፡ (ሉቃ.1፡59) ልጅ በስምንተኛው ቀን ለምን ይገረዛል? እግዚአብሔር ይህን ቀን ለምን መረጠው? ከሳይንሱ የቀደሙት ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ግዝረት ‹ዝቅ ብሎ በሰባት ቀን ቢፈጸም ‹ልህሉህ ስለሆነ ይጎዳዋል› ሲሉ ከስምንት ቀን አልፎ ዘጠኝ ከሆነ ደግሞ ይጠነክርበታል› ብለዋል፡፡
ሳይንሳዊው ማብራሪያም ከዚህ ጋር ይስማማል፡፡ በሰውነታችን ውስጥ እጅግ አስፈላጊ የሆኑ ቫይታሚን ኬ እና ፕሮትሮምቢን የሚባሉ ንጥረ ነገሮች አሉ፡፡ እነዚህ ንጥረ ነገሮች በሰውነታችን መኖራቸው ለደማችን መርጋት የግድ የሚያስፈልግ ነው፡፡ ሆኖም በተፈጥሮ እነዚህ ንጥረ ነገሮች መቶ በመቶ በሰውነታችን ውስጥ በበቂ መጠን ተሟልተው የሚኖሩት ከተወለድን ከስምንተኛው ቀን ጀምሮ ነው፡፡ በተለይ ፕሮትሮምቢንየተባለው ንጥረ ነገር ከመቶ ፐርሰንት በላይ ከፍ ብሎ የሚጨምርበት ብቸኛ ቀን ስምንተኛው ቀን ነው፡፡ ከዚያ ቀን በፊት ሕጻን ቢገረዝ ለአደጋ የሚጋለጥ ሲሆን ስምንተኛው ቀን ግን ቀዶ ሕክምና ያለ ስጋት ለማድረግ ሕጻኑ የሚሰማውን ሕመምም ለመቀነስ ወሳኝ ቀን ነው፡፡ ቀኑ ካለፈ ፕሮትሮምቢን ወደ መደበኛ ሥፍራው ይመለሳል፡፡ ስለ ፍጥረቱ የሚያውቀው ፈጣሪ ሳይንስና ሳይንቲስቶች ሳይኖሩ ያወጣው የኦሪት ሕግ መሆኑ ደግሞ የበለጠ ያስደንቃል፡፡
ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ዛሬ (ጥቅምት 22) ሰማዕት የሆነበት ዕለት ነው፡፡ ወደ ጻፈለትና ወደ ሣለው ጌታው ሔዶ የክብር አክሊልን ተቀዳጅቷል፡፡ ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ ዛሬ ወደ ላይኛው ባለ መድኃኒት ፣ ራሱም መድኃኒት ወደ ሆነው ፈጣሪ ሔዷል፡፡ ጌታችን ራሱን ‹‹ባለ መድኃኒት ሆይ ትሉኛላችሁ›› ብሎ የተናገረው ባለ መድኃኒቱ ሉቃስ በጻፈው ወንጌል ላይ ብቻ ነበር፡፡ (ሉቃ.4፡23)
ዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ
ጥቅምት 2011 ዓ.ም. ተጻፈ