14/01/2023
ዛሬ የገድለ-ዲያብሎስ የዝና ታሪክ፣ የኃጢአትና የሞት ዜና መረጃ በበዛበት ዓለም ውስጥ እንገኛለን፡፡ ኃጢአት፤ ለዚህ ዘመን ሰው የመጀመሪያው ዕውቀትና የሥነ-ምግባሩ መግለጫ በመሆን፤ ጸሎት ጽድቅንና እውነትን የባርነት መንገድ አድርጎ እንዲያይ፤ የትውልዱ የውድቀት ጉዳይ ፈጻሚ የመሆን ዕጣ ድርሻውን ከዲያብሎስ ተምሯል፡፡
‹‹በጎ እያደረጋችሁ፣ የማያውቁትን ሞኞች ዝም ታሰኙ ዘንድ እንዲህ የእግዚአብሔር ፈቃድ ነውና፤ አርነት ወጥታችሁ እንደ እግዚአብሔር ባሪያዎች ሁኑ እንጂ ያ አርነት ለክፋት መሸፈኛ እንዲሆን አታድርጉ፡፡›› 1ጴጥ 2÷15-16
ክፉ መናፍስት፤ በሕይወታችንና በኑሯችን ውስጥ፤ ሥፍራና ቦታ አግኝተው፤ በውድቀት አዙሪት ውስጥ እንድንኖር ሊያደርጉ የቻሉበት አንዱና ዓብይ ምክንያት፤ ለአምላካችን የቅድስና አምልኮትና ለእግዚአብሔር ጸሎት ባለማድረሳችን ነው፡፡
ከዲያብሎስ መሠረታዊ ሥልት አንዱ፤ በዓለማዊው መድረኮች ላይ ለመንፈሳዊ ሕይወት ቦታ እንዳይሰጥ፤ በተለይም ጸሎት ወደ እግዚአብሔር እንዳይደርግ ማዘናጋት ነው፡፡
ጸሎት አለማድረግ ደግሞ፤ ከእግዚአብሔር የሚያለያየን ዋንኛ መንገድ ነው፡፡ ዛሬ በዚህ ጎዳና ላይ እኛም እየተጓዝንበት እንገኛለን፡፡ ከአምላክህ ጋር ከተለያየህ ደግሞ፤ የምታዳብረው ጠባይ፤ ክፋትን፣ ተንኮልን፣ ፌዘኝነትና ደንታ ቢስነትን ወዘተ… ነው፡፡
በዚህ መንገድ ከተጓዝን ደግሞ፤ ጸሎት የለም፡፡ ምናልባት የምንሰማውና የምናየው የአንድና የሁለት ደቂቃ የሕሊና ጸሎት የሚባለውን ነው፡፡ የሚገርመው ግን፤ ይህ የሕሊና ጸሎት ለማን እንደሆነ፣ ምን ተብሎ እንደተጸለየና ማን እንደሰማው አለመታወቁ ነው፡፡
እንደዚህ ዓይነቱ ጸሎት፤ ዘመናዊው ሰው ምንጊዜም አቅጣጫውን ሲለውጥ፣ እምነቱን ሲጥል፣ የማንነት ጉዳዩን ከመናቅም በላይ፤ አዲስ ነገርና የፈጠራ ሃሳብ መሞከሪያ ሲሆን፤ እራሱን እያዘናጋ በሕይወት ተምሳሌቱና ከጊዜው እይታ ጋር ሲወዳደር፤ ለየግል ፍላጎቱ ከሥራ ጋር ሲባዝንና ሲሯሯጥ፤ በመሐል ሃይማኖቱንና እምነቱን በመዘንጋት፤ ለከባድ መቅሰፍት እንዲጋለጥ የሚያደርግ ነው፡፡
ጸሎት፤ ከእውነተኛ አምልኮ ጋር የሚሄደው፤ ‹‹አባታችን ሆይ! በሰማያት የምትኖር ስምህ ይቀደስ መንግስትህ ትምጣ ›› ብሎ የሚጀምር ሲሆን ነው፡፡
ታዲያ ኃጢአት የኃፍረተ-ቢስነት፣ የአመፃ፣ የርኩሰትና የመቅሰፍት ቁጣ መግለጫ ሆኖ መቀመጡን መሰማት ብቻ ሳይሆን፤ በዓይናችን እያየነው፤ መንፈሳዊው ግብራችንና አመለካከታችን፤ ከክፉው ዓለም አመጸኞች የማይለይበት ሁኔታ ውስጥ መገኘቱ፤ ብዙ ጊዜ ይስተዋላል፡፡
መንፈሳዊው አርአያነት ትኩረት ያልተሰጠው እንዲሆን፤ በክርስቶስ ርሕራሔና ቸርነት በይቅርታ በጸና፤ በፍቅር የጋራ ልብስ፣ በሃይማኖት ጥንካሬ፣ በዕውቀት የወንጌል ቃል ይዞታ ላይ የእግዚአብሔር ኃይል እንዳይገለጥ፤ በውስጡ የተደበቀ አጀንዳ ካለው ዲያብሎስ ጋር የሚቀራረብ፤ ቀደም ብሎ በመንፈሳዊውም ሆነ በዓለማዊውም መንገድ፤ ለክፋትና ለጥፋት ከሴራ ጋር ተቀናጅቶ የሚሄድ ወገንና አገልጋይ፤ ጥቂት አይደለም፡፡
የቅድስና አርዓያነት አለመኖር፣ የእምነት ማጣት ችግር፣ የመንፈሳዊ ጸጋ፣ በረከትና ክብር መራቅ፣ የታሪክ ጥላቻና የንቀት ተግባር፣ በአገልጋዮች ዘንድ ቦታ ከያዘ፤ የቤተሰብ መፍረስና የወላጆች መዋረድ፣ የዜጎች መኮብለልና ስደት፣ የሰው ልጆች ሥቃይ፣ እንግልትና ሞት ካላስደነገጠን፤ አገልጋዮች፤ በክርስቲያኑ ወገናችን ፊት መቆማችን፤ ትርጉም አልባ ይሆናል፡፡
ተደናግሮ ማደናገር የዘመናችን ሙያዊ ዘዴ፣ እንጀራ፣ ደሞዝና ኑሮ ሆኖ፤ የውድቀት ማቆያና የብልጣብልጥ የአቋራጭ መንገድ፤ ዕውቀትና ማዕረግ ሆኖዋል፡፡
╭══•|❀:✞✟✞❀|•══╮
✥┈┈••●◉✞◉●••┈••✥
ከ መልአከ ኃይል ቀሲስ ኃይለመለኮት ግርማ ወንድሙ
27/04/2015 ዓ.ም
ከሕይወት ተራራ ላይ መንፈሳዊነት ይብለጥ!
✥┈┈••●◉✞◉●••┈┈✥
╰══•|❀:✞✟✞❀|•══╯